የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ የትምህርት ግብዓት ፍላጎት አቅርቦትና ስርጭት ዳይሬክቶሬት በደጃዝማች ወንድይራድ ቅድመ 1ኛ አንደኛና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የልምድ ልውውጥ አካሄደ::
(ጥር 16/2017 ዓ.ም) የትምህርት ግብዓት ፍላጎት አቅርቦትና ስርጭት ዳይሬክቶሬት ከ11 ዱ ክፍለ ከተሞች የተመረጡ አምስት አምስት ትምህርት ቤቶች የትምህርት ቤት መሻሻል ምክትል ርእሳነ መምህራን እና የክፍለከተማ ምገባ ቡድን መሪዎችን በማሳተፍ በደጃዝማች ወንድራድ ቅድመ 1ኛ አንደኛና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በተማሪዎች ምገባ የከተማ ግብርናና ቆሻሻ አወጋገድ ዙሪያ የልምድ ልውውጥ አካሄዳል::
በልምድ ልውውጡ ላይ ተገኝተው ለተሳታፊዎች መልእክት ያስተላለፉት የቢሮው የትምህርት ግብዓት ፍላጎት አቅርቦትና ስርጭት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ምስራቅ ብርሀነመስቀል የምገባ ስርዓት ተማሪዎች በምግብ እጦት ትምህርታቸውን እንዳያቋርጡ ከማስቻል ባለፈ ተማሪዎች በአካልና በስነልቦና ብቁ ሆነው ትምህርታቸውን መከታተል ያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል ::
ዳይሬክተሯ አክለውም የከተማ አስተዳደሩ ቁርጠኛ አቋም በመያዝ ተማሪዎች ንቁ ሆነው ትምህርታቸውን መከታተል እንዲችሉ የምገባ ስርዓት መዘርጋቱ መንግስት ብቁ ዜጋ ለማፍራት እያደረገ ካለዉ ጥረት አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል :: አያይዘውም የልምድ ልውውጡ ተሳታፊዎች በደጃዝማች ወንድራድ ትምህርት ቤት ያሉ የአሰራር ስርዓቶች ወደራሳቸው በመውሰድ የምገባ ስርአቱን ቀድሞ ከነበረው በተሻለ ጥራትና ያለን የውስጥ አቅም በመጠቀም እንዲሰሩ ጠይቀዋል ::
በልምድ ልውውጡ ላይ የትምህርት ቤቱ ርዕሰ መምህር አቶ ሰለሞን ክቤ ለልምድ ልውውጡ ተሳታፊዎች የምገባ ሥርዓቱንና የከተማ ግብርናውን አስመልክቶ ሰነድ ያቀረቡ ሲሆን የምገባ ሂደቱ ጥራቱን የጠበቀ እንዲሆን የከተማ ግብርና መኖር ፣ የመጋቢ እናቶች ጤናማ የአመጋገብ ስርዓት እንዲፈጥሩ ተከታታይ ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንዲሁም ከሸማቾችና ንግድና ኢንዱስትሪ ጋር የስራ ትስስር መፍጠር ለምገባ ሥርዓቱ ስኬት የራሱ ሚና እንደነበረው ተናግረዋል::
የልምድ ልውውጡ ተሳታፊዎች የትምህርት ቤቱን የምገባ ስርዓትና አቅርቦት ፣ የከተማ ግብርናና ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓቶችን ጎብኝተዋል:: በትምህርት ቤቱ የምገባና የከተማ ግብርና ሥራዎች ላይ የተመለከቱትን ልምድም ወደራሳቸው ትምህርት ቤቶች በመውሰድ የተሻለ የምገባ ስርዓት ለመዘርጋት መነሳሳት እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል ::